Translate/ተርጉም

Tuesday, October 30, 2018

ሰላማችን በእጅ የያዙት ወርቅ አይሁን!


ሰላማችን በእጅ የያዙት ወርቅ አይሁን!
በአንድ ሀገር በተራራማ ሥፍራ የሚኖር አንድ ብልህ ሽማግሌ ነበር፡፡ ይህ ብልህ ሰው በየዕለቱ ከተራራው እየወረደ ባቅራቢያው ባለው መንደር በመግባት በልዩ ችሎታው የመንደሩን ሕዝብ በማዝናናት ይታወቃል፡፡ ከብዙ ልዩ ችሎታዎቹ መካከል አንደኛው አንድ ሰው በኪሱ ወይም በሻንጣው የያዘውን ነገር አውቆ በትክክል መናገሩ ነበር፡፡
ከዕለታት በአንዱ ቀን የተወሰኑ የመንደሩ ወጣቶች አውቃለሁ የሚለውን ነገር አሳስተው ሊቀልዱበት ፈለጉና አንደኛው ወጣት በእጁ ወፍ በመያዝ ወደ ሽማግሌው ቀርቦ ምን እንደያዘ እንደሚነግሩት ስለሚያውቅ አንድ ዕቅድ አሰበ፡፡ «በእጄ ምን እንደያዝኩ ያውቃሉ፣ ወፏ ሙታለች ወይስ በሕይወት አለች? ብዬ እጠይቃቸውና በሕይወት አለች ካሉኝ በመዳፌ ጭምቅ በማድረግ እገላትና አዋርዳቸዋለሁ፤ ወይም ደግሞ ሙታለች ካሉኝ እጄን በመክፈት ወፏ እንድትበር አደርጋለሁ። በዚህ መንገድ አለማወቃቸውን አሳያቸዋለሁ» እያለ እቅዱን አዘጋጀ።
በማግስቱ ሽማግሌው እንደተለመደው ወደ መንደሩ ሲገቡ እጁን ወደ ኋላ አጣምሮ በመያዝ «በእጄ ምን እንደያዝኩ ይንገሩኝሲል ሽማግሌውን ጠየቃቸው፡፡ ሽማግሌው በፍጥነት «ወፍ ይዘሃል» በማለት መለሱለት፡፡ ልጁ አሁንም ጠየቀ «የያዝኳት ወፍ በሕይወት አለች ወይስ ሙታለችአላቸው። ሽማግሌው ወጣቱን ትኩር ብለው እየተመለከቱ እንዲህ በማለት መለሱለት።
«ወፊቱ ባንተ መዳፍ ቁጥጥር ውስጥ ናት:: አንተ እንድትሆን በምትፈልገው ትሆናለች:: አየህ ልጄ! ይሄ አሁን ያደረከው ተግባር በሕይወት መንገድህም ቢሆን ያተገባበር መርህነቱ የተጠበቀ ነውና በሕይወትህም በተመሳሳይ ሁናቴ ይተገበራል፡፡ ወፊቱን ማዳንም ሆነ መግደል እንደምትችል የምታውቀው አንተው እራስህ ነህ። ለሕይወትህ ማማርና ለኑሮህ መለወጥም ቢሆን እድሉ ያለው በመዳፍህ ላይ ነው፤ በእጅህ ውስጥ ነው ያለው» በማለት ያሰበውን ሳይቀር በምሳሌ አስረዱት። በርግጥም የሕይወታችንን መንገድ የምንጠርገው እኛው እራሳችን ነን። የዛሬ መንገዳችን የነገ መድረሻችንን እንደሚወስነው ሁሉ በመዳፋችን የያዝነው ማንኛውም ነገር ላይ ውሳኔ ማሳረፍ የምንችለው ራሳችን እንደሆን ማመን ይገባናል።
ሀገራችን በመውጣትና በመውረድ ውስጥ ዘመናትን አሳልፋለች። በመውጣቷም ሆነ በመውረዷ ውስጥ ዜጎቿ አለን። ለዚህም ነው በእድገቷም ሆነ በውድቀቷ ተጠያቂም ሆነ ተመስጋኝ የምንሆነው። ዛሬ በሀገራችን ከፍተኛ የለውጥና የመነቃቃት ንፋሶች በመንፈስ ላይ ናቸው። በሁሉም ማዕዘናት ተስፋዎችን እያየን ነው። ተስፋዎቻችን እውን ይሆኑ ዘንድ ደግሞ መልካም አስተሳሰቦቻችን አደርጅተንና አስተባብረን ልንጠቀምባቸው ይገባል። ከምንም ነገር በላይ የሁሉም ነገራችን ቁልፍ የሆነውን ሰላማችንን ልናስጠብቀው ይገባል። ካልሆነ ግን በእጅ እንደያዙት ወርቅ ሆኖ ሳንጠቀምበት በመቅረታችን ልንቆጭበት እንደምንችል መዘንጋት የለብንም።
ችግሮቻችን ውስብስብና በርካታ ናቸው። ለዚህም ነው ፈጥነን ወደ መረጋጋትና ወደ ሰላም ለመግባት ያልቻልነው። አንድ አካባቢ ያለው ችግር ሲፈታ ሌላው አካባቢ ይታወካል። ለዚህ መውጣትና መውረድ ምክንያቱ ግልፅ ነው። በአንድ በኩል በርካታ ለውጥ ፈላጊዎችና የለውጥ አራማጆች እንዳሉ ሁሉ ለውጡን ለማደናቀፍ የሚፈልጉይሎች በሌላው ወገን በመኖራቸው በሰላም ውለን በሰላም እንዳንገባ የጥል ሰበካቸውን ያጧጡፉታል። የአዛውንቱ ምክርም ይህንን ሀሳብ ይበልጥ እንድንረዳው ያደርገናል። ምክንያቱም ሰላም ሆነ እረብሻው በመዳፋችን ውስጥ ነው ያለው። የሚለየው የአጠቃቀማችን ሁኔታ ነው።
«ታላቅ አገር የመገንባት ህልማችንን እውን ለማድረግ ከሰላም ውጪ ምንም አቋራጭም ሆነ አማራጭ የለንም፡፡ ሁላችንም ሰላማችንን አጥብቀን እንድንጠብቅ ከሁሉ በላይ ሰላም ሲታወክ በምትሰቃየዋ በእናት ሥም አጥብቄ እጠይቃችኋለሁ!››ያሉት አዲሷ ፕሬዚዳንት ሣህለወርቅ ዘውዴ ካለ ምክንያት አይደለም። የሰላም እጦት ዋነኛ ተጠቂዎች ሴቶች በመሆናቸው ነው። በሥልጣን ቆይታቸው ዋነኛው ትኩረታቸው መላው ኢትዮጵያን ሴቶችና ሰላም ወዳድ ወንዶችን እንዲሁም በመላው ዓለም የሚገኙ ሰላም ወዳዶችን ሁሉ ከጎናችው በማሰለፍ ሰላም በማስፈን ላይ ርብርብ ማድረግ እንደሚሆንም አስታውቀዋል። ምክንያቱም ካለ ሰላም ምንም አይነት እድገትም ሆነ ልማት ሊኖር አይችልምና።
ሰላም የህልውና መሰረታችን ነው፤ ለአንድ ሀገር ልማትና እድገት ሰላም ከማንምና ከምንም በላይ የገዘፈ ዋጋ እንዳለው ልንረዳ ይገባል፡፡ የሰላምን ዋጋ በምንም አይነት ምድራዊ ስሌት ልናሰላው አንችልም፤ በሀገርም ሆነ ከግለሰብ የማደግና የመለወጥ ህልም ጀምሮ እስከ ሀገር ልማት ድረስ ሰላም ከደፈረሰ የቱንም አይነት የመደመርና የለውጥ አራማጆች ቁጥር ቢበዙ ወደ ምንመኘው ልማት መጓዝ አይቻለንም።
ለዚህ ነው በመዳፋችን ውስጥ ያለውን የሰላም ዋጋ ከከበሩ ድንጋዮች አልቀን እንድንጠቀምበት የሚጠበቀው። ስለሆነም አካባቢያችን፣ አልፎም ሀገራችን የሰላም አየር የነፈሰባት ዜጎቿ በሰላም ወጥተው የሚገቡባት እንድትሆን ከእያንዳንዳችን ብዙ ይጠበቃል። በመዳፋችን ያለውን የመደመር እሳቤ የለውጥ እንቅስቃሴ ለመጠበቅና ለማስጠበቅላፊነታችንን መወጣት አለብን። በመዳፋችን ውስጥ የያዝነውን ሰላማዊ አስተሳሰብ ለማንም አሳልፈን መስጠት የለብንም።

No comments:

Post a Comment