Translate/ተርጉም

Tuesday, October 30, 2018

እንደ አሸን ይፈላሉ፤ እንደ ጤዛ ይረግፋሉ!


እንደ አሸን ይፈላሉ፤ እንደ ጤዛ ይረግፋሉ!
ዋለልኝ አየለ
ለካ ስማቸውን እንኳን የማናውቀው ምን ያህል ጋዜጦችና መጽሔቶች አሉ ጎበዝ? እኔ እኮ ሰሞኑን ነው ጉዴን ያየሁት! በእርግጥ ቀደሙኑም ቢሆን አንባቢ ነኝ ብዬ አልተመጻደቅኩም፤ ያም ሆኖ ግን ስማቸውን እንኳን የማላውቀው ይህን ያህል ጋዜጦችና መጽሔቶች ይኖራሉ ብዬ አላወቅኩም ነበር፡፡ ደግሞ እኮ በቅርብ ጓደኞቼ የጋዜጣና መጽሔት አንባቢ ተደርጌ ነበር የምታሰበው፡፡ እኔ ራሱ እኮ እውነት መስሎኝ ‹‹እባካችሁ ጋዜጣና መጽሔት አንብቡ›› እያልኩ ስመክር ነበር(እኔን ብሎ መካሪ!)
ሰሞኑን ከአንድ ጓደኛዬ ቤት ገብቼ ነበር፡፡ አንድ እስከመኖሩም የማላውቀው ጋዜጣና ብዙ መጽሔቶች አገኘሁ፡፡ በቃ ሥራዬ መጽሔቶችን እያነሳሁ ‹‹እንዲህ የሚባልም ነበር እንዴ?›› ማለት ሆነ ስራዬ፡፡ በነገራችን ላይ በመጽሔት እንጂ በጋዜጣ ግን ብዙም የማላውቀው አላጋጠመኝም፡፡
መጽሔቶችና ጋዜጦች የሚሸጡባቸውን አካባቢዎችም(በብዛት አራት ኪሎና ፒያሳ) አስተውዬ ነበር፡፡ የምር ብዙ አዳዲስ የህትመት ውጤቶች ወደ ገበያ ገብተዋል፡፡ እንዲያውም አንድ ጋዜጣ ስመጥር እየሆነ ነው፡፡ የጋዜጦች ነገር ገበያ ላይ ያሉት ብቻ አይደሉም፡፡ ልብ ብላችሁ ከሆነ በማህበራዊ ድረ ገጾች አዳዲስ ጋዜጦች ሊጀመሩ እንደሆነም እየተዋወቀ ነበር፡፡ አሁን እንግዲህ ያ ‹‹እንደ አሸን ፈሉ›› የሚባለው አገላለጽ ሊደገም ነው ማለት ነው፡፡ ይሄን ቃል ግን የምናውቀው ኢህአዴግ ስለግል ፕሬስ ሲያወራ ነው አይደል? መንግስት «እንደ አሸን የፈሉ የግል የህትመት ውጤቶች ይላል»፤ እነርሱ ደግሞ «ኢህአዴግ ነው እንደጤዛ የሚያረግፈን» ይላሉ፡፡
እኔ ግን የሁለቱም ወሬ አልተመቸኝም (እንደ አንባቢ እንዲህ ማለት መብቴ ነው)፡፡ መንግስት አምስት የግል ጋዜጣ እንኳን በሌለበት ‹‹እንደ አሸን የፈሉ›› ይላል፡፡ ቆይ ግን እንደ አሸን የፈሉ የሚለው ቃል ለአንድና ለሁለት ጋዜጣም ይሰራል እንዴ? በዚያ ላይ ኮሽ ባለቁጥር የፖለቲካ ጋዜጦችን እየዘጉ እንደ አሸን ይፈላሉ ማለት ሹፈት ነው፡፡
መንግስት እኮ ቢያውቅ እንዲህ ማደረግ አልነበረበትም (እኔ ልምከረዋ እንግዲህ!) ለምሳሌ ጋዜጦቹን የሚዘጋው ለምን ይተቹኛል ብሎ ነው አይደል? መተቸት እኮ የሚያሳየው የመንግስትን ዴሞክራሲያዊነትን ነበር፡፡ ለዴሞክራሲያዊነቱ እነዚያ መንግስትን የሚያብጠለጥሉ ጋዜጦች ምስክር ናቸው ማለት ነው፡፡ ምክንያቱም ነጻነት ተሰጥቷቸው ነው የሚተቹት፡፡ ይህ ነገር ቢለመድ እኮ ህዝቡም ትችት አዲስ አይሆንበትም ነበር፡፡ መታፈን ከበዛ ግን ጥሩ አይሆንም፡፡ አንድ ምሳሌ ልስጣችሁ፡፡
አንድ የስነ ጽሑፍ መድረክ ላይ ስለፍቅረኛ የተጻፈን ግጥም ሰው እንደምንም ጠምዝዞ የፖለቲካ ትርጉም ይሰጠዋል፡፡ ግልጽ የሆነው ትርጉም እያለ ሌላ ተደራቢ ትርጉም ፍለጋ ይሄዳሉ፡፡ መንግስትን የምትነካ አንድ ቃል ካለች ያላቋረጠ ጭብጨባ አዳራሹን ያደበላልቀዋል፡፡ ይሄ የሚያሳየው መተቸት ብርቅ መሆኑን ነው፡፡ በጋዜጦችና መጽሔቶች የተለመደ ቢሆን ኖሮ እንኳን እያጣመሙ መተርጎም በግልጽ የተባለውም ብርቅ አይሆንም ነበር፡፡
እነርሱም ቢሆን ችግር አለባቸው፡፡ «እንደጤዛ ያረግፈናል» ይላሉ እንጂ አንዳንዶቹ የረገፉት ራሳቸው ነው፡፡ በተለይ መጽሔቶች መንግስት ከሚዘጋቸው ይልቅ በአቅም እጦት የሚዘጉት ናቸው የሚበልጡት፡፡ ይሄ ግን የእነርሱ ብቻ ሳይሆን ራሱ የማህበረሰቡም ችግር ነው፡፡ ጋዜጣና መጽሔት አድኖ የሚገዛ ማህበረሰብ አይደለም ያለን፡፡ ስንትና ስንት አገራዊ ጉዳዮች ወጥተው ‹‹ምን ጋዜጣ አለና!›› ብሎ በጭፍን የሚተች ማህበረሰብ ነው ያለን፡፡
የራሳቸው የመጽሔቶችና ጋዜጦች ችግርም ቀላል አይደለም፡፡ በተለይ መጽሔቶች ያናድዱኛል፡፡ በተለይ አሁን አሁንማ የማህበራዊ ገጾችን ገልብጦ ማሳተም ተለመደ፡፡ መጽሔትን ያህል ነገር እንዴት የፌስቡክ ወሬን እንደ ትልቅ ጉዳይ ይዞ ይወጣል? ትልልቅ ትንታኔና ቃለ መጠይቅ ቢሆን አዲስ ነገር ሊኖረው ይችላል፡፡ ፌስቡክ ላይ ሲመላለስ የቆየ ጉዳይ በ15 ቀን የሚታተም መጽሔት ላይ እንዴት ዜና ሊሆን ይችላል? ዜናቸው ደግሞ ‹‹ውስጥ አዋቂ ምንጮች እንደገለጹት፣ ስማቸውን መናገር ያልፈለጉ ሰዎች እንደገለጹት፣ የአይን እማኞች እንደገለጹት…›› የሚል ነው፡፡ ምርጥ የምርመራ ዘገባ ቢሰራ እኮ ጋዜጦችና መጽሔቶች ታድነው ይገዙ ነበር፡፡ ሌላው ችግራቸውም ብሔርን ከብሔር የሚያጋጩ ነገሮች ላይ ጥንቃቄ አለማድረግ ነው፡፡ ማህበረሰባችን ነገሮችን ቀለል አድርጎ ማየት አለመደም፡፡ እውነት ቢሆን እንኳን ለደህንነት ተብሎ የማይነገር ነገር ሊኖር ይችላል፡፡
ስማቸውን መግለጽ ያልፈለጉ ሰዎች የሚለውን ችግር ግን አሁንም ወደ ማህበረሰቡ ልወስደው ነው (ማህበረሰብ አይተችም ያለው ማነው?) ይሄ ‹‹ምን ጋዜጠኛ አለና ነው!›› እያለ የሚያማርረው ሁሉ ካሜራና መቅረጸ ድምጽ ሲያይ ‹‹ምን አገባኝ›› የሚል ነው፡፡ የመንግስት ጋዜጠኛውን «የመንግስት ተላላኪ»፤ የግሉንም «የተቃዋሚ ተላላኪ» እያለ የሚሳደበው ሁሉ እስኪ ተናገር ቢባል አይናገርም፡፡ ጀግና ማለት ግን ተናግሮ የሚመጣውን የሚቀበል ነው፡፡ አንዳንዱ ደግሞ ጉዳዩ እንዲነገርለት ይፈልግና ግን ስሜን እንዳትጠቅሱ ይላል፡፡ ስለዚህ ያለው አማራጭ ስሙን መደበቅ ነው፡፡
እንግዲህ የጠቅላይ ሚኒስቴር ዶክተር አብይ አህመድን ወደ ስልጣን መምጣት አስመልክቶ በተደረገው የይቅርታና የመደመር መርህ ይመስላል አሁን ደግሞ እንደ አዲስ ጋዜጦችና መጽሔቶች እየተፈጠሩ ነው፡፡ 2006 .ም ላይ አምስት የህትመት ውጤቶች በአንድ ጊዜ ሲዘጉ በግሉ ፕሬስ ዘንድ ድንጋጤን ፈጥሮ ነበር፡፡ ከዚያ በፊትም ምርጫ 97ን ተከትሎ ብዙዎች ተዘግተዋል፡፡ በየመሃሉ ደግሞ በአቅም እጦት ይሁን በመንግስት ጫና ባይታወቅም ዝም ብለው ከገበያ ላይ የጠፉ የህትመት ውጤቶች ነበሩ፡፡ በየመድረኩም የግሉ ፕሬስ ጉዳይ በተነሳ ቁጥር መንግስት ጫና አድርገሃል እየተባለ ተወቅሷል፡፡
እስኪ አሁን እንግዲህ እንደ አሸን ሊፈሉ ነውና የመንግስትንም ዴሞክራሲያዊነት፣ የፕሬሶችንም ጥንካሬ እናያለን፡፡ እኔ ግን ከዚህ በላይ ያጓጓኝ የዚህ በጭፍን የሚሳደበው ነገር ነው፡፡ የአንድ ጋዜጣ ወይም መጽሔት ስም ሳያውቁ መንግስትንም ሆነ አዘጋጆችን መተቸት አላዋቂነትን ነው የሚያሳየው፡፡ ይሄ ጨቋኝ የሆነ መንግስት የሚል ሰው አንድ የተዘጋ ጋዜጣ ስም ጠርተህ እስኪ ምን ዘገባ ይዞ ወጥቶ ነበር ብትለው እስከስሙም አያውቀውም፡፡ ከጃምቦ ቤት የተረፈው ጊዜም የሚውለው ማህበራዊ ገጾች ላይ ነው፡፡ ስለዚህ ኃላፊነቱ የሁላችንም ነው፡፡ መንግስትም ሀገሪቱ ይህን ያህል የህትመት ውጤቶች አሏት ተብሎ ይመስገን! እኛም አንባቢዎች ከወቀሳ እንዳን!


No comments:

Post a Comment